Posts filter


https://youtube.com/playlist?list=PLmCrONGfZd8RYMGzfdniy7o9Cjxar1b6f&si=sRTio5bsTP0Yf1MM
ምክረ ሕግ
የተሻሻለው የገጠር መሬት አስተዳደርና አጠቃቀም አዋጅ /1324/16/ (ክፍል -1)




ምክር ቤቱ የቀረቡለትን ረቂቅ አዋጆች መርምሮ አጸደቀ።

ባሕር ዳር: የካቲት 07/2017 ዓ.ም የአማራ ብሔራዊ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር፣ 4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 9ኛ መደበኛ ጉባኤ የቀረቡለትን ረቂቅ አዋጆች እና ረቂቅ ደንብ መርምሮ አጽድቋል።

የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ዓለምአንተ አግደው ረቂቅ አዋጆችን ለምክር ቤቱ አቅርበዋል። ረቂቅ አዋጆቹ ፍርድ ቤቱ የጀመራቸውን የለውጥ ሥራዎች ስኬታማ እና ዘላቂ ለማድረግ፣ ዘመኑን እንዲዋጅ እና የዳኝነት ሥርዓቱን የተሳካ ለማድረግ ያስችላሉ ነው ያሉት።

የዳኝነት ሥርዓቱን ነጻ እና ገለልተኛ ለማድረግ፣ አዳዲስ እና አዳጊ ሃሳቦችን ለማስተናገድ እንደሚያስችልም አንስተዋል።

የዳኝነት ሥርዓቱን ነጻ እና ገለልተኛ ማድረግ ግድ እንደሚልም ተናግረዋል። የፍትሕ ሥርዓቱን ጠንካራ ለማድረግ እና የሕዝብን ጥያቄ ለመመለስ እንደሚያስችልም አብራርተዋል።

የአማራ ክልል ሕዝብ በባሕላዊ እሴቶች የመዳኘት ፍላጎት እና ልምድ እንዳለው ያነሱት ፕሬዝዳንቱ ለባሕሉ ዕውቅና መስጠት እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል።

ጊዜን እና ወጭን እንደሚቆጥብ፣ የመደበኛ የዳኝነት ሥርዓቱን ሥራ እንደሚያቀል እና ዘላቂ ሰላምን እንደሚያሰፍንም ተናግረዋል።

የምክር ቤቱ የሕግ፣ ፍትሕ እና አሥተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሠብሣቢ ደሴ ጥላሁን (ዶ.ር) ፍርድ ቤቱ የተቋም ግንባታውን ለማጠናከር እና የጀመራቸውን የለውጥ ሥራዎች የተሳካ ለማድረግ እንደሚረዱት ተናግረዋል።

የቀረቡት ረቂቅ አዋጆች የነበረውን የሕግ ክፍተት የሚሞሉ መኾናቸውን ነው የተናገሩት። ጠንካራ የዳኝነት ሥርዓት እንዲኖር ረቂቅ አዋጆቹ አስፈላጊ መኾናቸውን አንስተዋል።

የምክር ቤት አባላትም ረቂቅ አዋጆቹ አሳሪ ሕጎችን እንደሚያሻሽሉ ተናግረዋል። ረቂቅ አዋጆቹ ፍርድ ቤቱ የጀመራቸውን የለውጥ ሥራዎች ለማስቀጠል እንደሚያግዘውም ገልጸዋል። የዳኝነት ሥነ ምግባርን ማስተካከል እና ፍትሐዊ የኾነ የዳኝነት አገልግሎት መስጠት እንደሚገባም አመላክተዋል።

ምክር ቤቱ መርምሮ ያጸደቃቸው ረቂቅ አዋጆች:- የአማራ ክልል ፍርድ ቤቶች ማጠናከሪያ ረቂቅ አዋጅ፣ የአማራ ክልል የባሕል ፍርድ ቤቶችን ለማቋቋም እና ዕውቅና ለመስጠት የወጣ ረቂቅ አዋጅ፣
የአማራ ክልል ፍትሕ እና የሕግ ኢንስቲትዩት እንደገና ማቋቋሚያ ረቂቅ አዋጅ፣የአማራ ክልል ፍርድ ቤቶች የዳኝነት አገልግሎት ክፍያ ለመወሰን የወጣ ረቂቅ ደንብ ናቸው።






ምክር ቤቱ የዳኞችን ሹመት አጸደቀ።

ባሕር ዳር: የካቲት 07/2017 ዓ.ም ፦ የአማራ ብሔራዊ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር፣ 4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 9ኛ መደበኛ ጉባኤው የፍርድ ቤት ዳኞችን ሹመት አጽድቋል።

ምክር ቤቱ ሹመታቸውን ያጸደቀው የፍርድ ቤት ዳኞች 3 ዳኞች ለከፍተኛ ፍርድ ቤቶች
ፕሬዝዳንት፣9 ዳኞች ለጠቅላይ ፍርድ ቤት፣46 ለከፍተኛ ፍርድ ቤት ዳኞች፣171 ዳኞች ለወረዳ  ፍርድ ቤት ዳኞች ናቸው።

ምክር ቤቱ  ከባድ የሥነ ምግባር  ጥሰት የፈጸሙ ሁለት ዳኞችን ለሦስት ዓመታት ከሥራ አግዷል።


የአማራ ክልል ጋዜጠኞች ማህበር


የክልል ምክር ቤቱ ሶስት አዋጆችን አፀደቀ

ባሕር ዳር፤ የካቲት 6/2017ዓ.ም፦ የአማራ ክልል ምክር ቤት በዘጠነኛ መደበኛ ጉባዔው ሶስት አዋጆችን አፀደቀ።

ምክር ቤቱ ያጸደቃቸው አዋጆች የመንግስት የአስተዳደር ስነ-ስርዓት አዋጅ፣ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ማሻሻያ አዋጅ እና የጥብቅና አገልግሎት ፈቃድ አሰጣጥና አስተዳደር ማሻሻያ አዋጅ ናቸው።

የክልሉ ፍትሕ ቢሮ ኃላፊ አቶ ብርሃኑ ጎሽም የመንግስት የአስተዳደር ስነ-ስርዓት አዋጅ የመንግስት አመራር ተጠያቂነት በሚያረጋግጥ ለሕግ የበላይነት መረጋገጥ ወሳኝ ነው ብለዋል።

አዋጁ በአስተዳደር ተቋማት የሚሰጡ ውሳኔዎችና የሚወጡ መመሪያዎች በሰዎች መብቶችና ጥቅሞችን በህግ እንዲመሩ ያስችላልም ነው ያሉት።

በውሳኔዎች ቅር የተሰኘ ግለሰብ የውሳኔዎቹንና የመመሪያዎቹን ህጋዊነት በፍርድ ቤት የሚያስመረምርበት ስርዓት በመደንገግ አስተዳደራዊ ፍትህን ማረጋገጥ እንደሚያስችልም እንዲሁ።

የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ማሻሻያ አዋጅ የመንግስት አሰራር ግልፅነትና ተጠያቂነት ይበልጥ እንዲጠናከር እንደሚያግዝ ጠቅሰዋል።

የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶችን ተጠያቂነት እና የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ድርጅቶቹ ስራቸውን በሕግ አግባብ እንዲያከናውኑ ያስገድዳልም ነው ያሉት።

በህብረተሰቡ ዘንድ የበጎ አድራጎትና የበጎ ፈቃደኝነት አገልግሎት ባህል እንዲዳብር የአዋጁ መውጣት አስፈላጊ እንደሆነም አብራርተዋል።

የጥብቅና አገልግሎት ፈቃድ አሰጣጥና አስተዳደር ማሻሻያ አዋጅም የህዝብን ጥቅም ለማስጠበቅና ፍትህን ለማስፈን እንደሆነም ገልጸዋል።

የህግ የበላይነትን ለማረጋጋጥና የፍትህ ስርዓቱን መሠረታዊ ዓላማዎች ከግብ ለማድረስ ጠበቆች፣ የጥብቅና አገልግሎት ድርጅቶች የሚመሩበትን ስርዓት መዘርጋት አስፈላጊ እንደሆነ ጠቁመዋል።

የምክር ቤቱ የሕግ፣ ፍትህና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደሴ ጥላሁን (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ አዋጆቹ የተለያዩ መድረኮችን በማዘጋጀት ግብዓት በማሰባሰብ እንዲዳብሩ መደረጉን ተናግረዋል።

በተለይ የአስተዳደር ስነ-ስርዓት አዋጅ የአስተዳደር ፍትህ እንዲሰፍን የጎላ ፋይዳ እንዳለው አብራርተዋል።

የጥብቅና አገልግሎት ፈቃድ አሰጣጥና አስተዳደር አዋጅም ጠበቆች ፈቃድ ባወጡ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ የደንበኞች መድህን ዋስትና እንዲገቡ ያስገድዳል ብለዋል።

ይህም በደንበኞች፣ በመንግስትና በጠበቆች መካከል መልካም የስራ ግንኙነት እንዲፈጠር ድርሻው የጎላ መሆኑን አስስረድተዋል።

ምክር ቤቱም በአዋጆቹ ላይ በስፋት ከመከረ በኋላ አፅድቋል።
ኢዜአ




ስለይቅርታ ሕጉ ምን ይላል?

ባሕር ዳር: ጥር 20/2017 ዓ.ም ይቅርታ በወንጀለኛ መቅጫ ሕጉ አንቀጽ 229፣ በሀገሪቷ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 28፣ በአማራ ክልል ደግሞ የይቅርታ ጉዳይ የሕግ ማዕቀፍ የተሰጠው አዋጅ ቁጥር 136/1998 እና ይህን ለማስፈጸም የወጣው መመሪያ ቁጥር 30/2010 ላይ ሰፊ የሕግ ማዕቀፋ የተበጀለት ጉዳይ ነው።

ስህተት ሰዋዊ ባህሪ ነው። በዕለት ከዕለት መስተጋብርም ስህተት የሚጠበቅ ክስተት ነው። በዚያም ምክንያት አድማሱን አስፍቶ ወደ ግጭት፣ አለመስማማት እና ከፍ ሲልም ወደ ወንጀል የሚደርስበት አጋጣሚ ይፈጠራል።

ይህን ሰዋዊ ባህሪ ለመሻገር እና ለመሻር ይቅርታ ፍቱን መድኃኒት ነው። ይቅርታ ትልቅነት ነው። በሕግም የሚደገፍ ተግባር ነው።

አቶ ንጉሴ ዘገየ በምሥራቅ ጎጃም ዞን የወንጀል ዐቃቤ ሕግ ናቸው። ይቅርታ አንድ ሰው ለፈጸመው ወንጀል ወይም በደል የተጣለበትን ቅጣት ለመቀነስ እና በዚሁ ምክንያት ያጣቸውን መብቶች እና ጥቅሞች ለማስመለስ በመንግሥት አሥፈጻሚ አካላት የሚወሰድ እርምጃ ነው ይላሉ።

በሀገራችን እንደ ባሕልም ይቅርታ አንድ የበደለ አካል ተበዳዩን ያጠፍሁትን ጥፋት ይቅር በለኝ ብሎ በራሱ ተነሳሽነት ጥያቄ የሚያቀርብበት ክንውን ነው ብለዋል።

ወደ መደበኛው የወንጀል ተግባር እና ይቅርታ አሰጣጥ ሥርዓቱ ስንወስደው ደግሞ ይላሉ አቶ ንጉሴ ዘገየ በተለያየ አጋጣሚ ወንጀል የሠራ አካል ተገቢው ምርመራ ተደርጎበት እና የጥፍተኝነት ውሳኔ ከተላለፈበት በኋላ ውሳኔው ወይም የቅጣት ዘመኑ ከማለቁ በፊት በይቅርታ ነጻ የሚኾንበትን መንገድ የሚመለከት ነው።

የይቅርታ አሰጣጥ ሥርዓቱ ሂደት አለው የሚሉት ዐቃቤ ሕጉ ይቅርታ ጠያቂው ለሚመለከተው የመንግሥት አካል የይቅርታ ጥያቄ ያስገባል።

ጉዳዩ የሚመለከታቸው እና በየደረጃው ያሉ የይቅርታ አደረጃጀት ኮሚቴዎችም የወንጀል ፈጻሚውን የይቅርታ ጥያቄ በሚገባ ያጤኑታል ነው ያሉት።

ይቅርታ ከመደረጉ በፊት መጣራት ያለባቸው ጉዳዮች ሂደታቸውን ተከትለው እንደሚጓዙም ያነሳሉ።

በኮሚቴዎች ሲታይ የቆየው ጉዳይም እንደገና በክልል የይቅርታ መርማሪ ቦርድ አማካኝነት የግለሰቡ ጉዳይ ለይቅርታ ያበቃዋል ወይስ አያበቃውም የሚለው ነገርም ይታያል ብለዋል።

የመርማሪ ቦርዱ ውሳኔውን ለመሥተዳደር ምክር ቤቱ የደረሰበትን ውጤት ያደርስ እና የክልል መሥተዳድር ምክር ቤቱ ጉዳዩን ካየ በኋላ ይቅርታ እንዲሰጠው ይኾናል ሲሉ እንደ ክልል በሥራ ላይ ያለውን አካሄድ አንስተዋል።

በፌደራል ደረጃም ቢኾን አካሄዱ ተመሳሳይ ይዘት ያለው እንደኾነ አንስተዋል። በፌደራል ፍርድ ቤቶች በኩል የቀረበው የወንጀለኛ ጉዳይ ለፌደራል የይቅርታ መርማሪ ቦርድ ቀርቦ ጥያቄውን በውል ካጣራ በኋላ ውሳኔውን ለርእሰ ብሔሩ ይቀርባል ይላሉ።

በፌደራል ደረጃ ይቅርታ የሚሰጡት በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 79 መሠረት ርእሰ ብሔሩ ናቸው ነው ያሉት።

ስለዚህ ይቅርታው የመጨረሻ የሚሰጠው በክልል ደረጃ በክልል መሥተዳድር ምክር ቤቱ ሲኾን በፌደራል ደረጃ ደግሞ በርእሰ ብሔሩ እንደኾነ ተናግረዋል።

የይቅርታ ዓላማው በዋናነት የሕዝብን፣ የመንግሥትን እና የታራሚዎችን ጥቅም ለማስጠበቅ ሲባል ታራሚዎች በፈጸሙት ጥፋት ተጸጽተው እና ታርመው አምራች እና ሕግ አክባሪ ዜጋ እንዲኾኑ ማስቻል እንደኾነ የአማራ ክልል የይቅርታ አሰጣጥ እና አፈጻጸም መመሪያ ቁጥር 30/2010 ዓ.ም የወጣው መመሪያ ያስገነዝባልም ብለዋል።

አንድ ታራሚ 20 ዓመት የተፈረደበት ቢኾን ይህን ሁሉ ጊዜ በማረሚያ ቤት ከሚያሳልፍ ሕግ የሚያዘውን ሁሉ ያሟላ ታራሚ ወደ ሕዝቡ ቢቀላቀል ጥቅሙ ዘርፈ ብዙ ነው ይላሉ አቶ ንጉሴ ዘገየ።

ይህ የሚኾነው ግን በየደረጃው ያሉ የይቅርታ መርማሪዎች ተገቢነቱን ካረጋገጡ ብቻ እንደኮነም ጠቁመዋል።

የሕግ ባለሙያው አንድን የሕግ ታራሚ ለይቅርታ የሚያበቁ ጉዳዮች ብለው ያነሷቸው መመሪያ 30/2010 መሠረት የዕድሜ ልክ እስራት የተፈረደበት ሰው ወንድ ከኾነ እና 12 ዓመታት ከታሰረ፤ ሴት ኾና ደግሞ 10 ዓመታት ከታሰረች በዃላ ይቅርታውን ለመጠየቅ ቅድመ ኹኔታውን ያሟሉ እንደኾነ በሕጉ ተቀምጧል ብለዋል።

ሌላው ከዕድሜ ልክ እስረኞች ውጭ ቅጣት የተጣለባቸው ፍርደኞች ደግሞ አጠቃላይ ከተፈረደባቸው ውስጥ አንድ ሦስተኛውን ከታረሙ ይቅርታ ለመጠየቅ ቅድመ ኹኔታውን እንደሚያሟሉ ጠቁመዋል።

በሐሰተኛ ማስረጃ የተፈረደባቸው ግለሰቦች ከጊዜ በኋላ ወንጀሉን እንዳልፈጸሙ ተረጋግጦ ሲገኝ ያለምንም ቅድመ ኹኔታ የይቅርታው ተጠቃሚ ይኾናሉ።

የወንጀል ሥነ ሥርዓት ሕጉ ይህን ጉዳይ ስለማይመልሰውም የይቅርታ መመሪያው ይህን መፍታቱ መልካም ያደርገዋል ይላሉ።

እንደ ሕግ ባለሙያው ገለጻ ፍርደኞች ባይጠይቁም እንኳ መንግሥት በራሱ ተነሳሽነት ይቅርታ የሚያደርግባቸው አጋጣሚዎች እንዳሉም አንስተዋል።
ለአብነት ያነሱት መንግሥት የግለሰቦቹ በይቅርታ መፈታት ለሕዝብ ጥቅም አሰፈላጊ ናቸው ብሎ የሚያምንባቸው ከኾነ ነው ብለዋል።

ከዕድሜ ጋር በተያያዘም ዕድሜያቸው ከ15 ዓመት በታች ያሉ እና ከተፈረደባቸው ውስጥ ወንዶች አንድ አራተኛውን ሴቶች ደግሞ አንድ አምስተኛውን እርምት ከወሰዱ የይቅርታው ተጠቃሚ ይኾናሉ ብለዋል።

ዕድሜያቸው 60 ዓመት የኾናቸው ወንዶች ከተፈረደባቸው ውስጥ 10 ዓመት ከታረሙ፣ ሴቶች ደግሞ 55 ዓመት ኾኗቸው ስምንት ዓመት እርምት ከወሰዱ ይቅርታ ይደረግላቸዋል ይላል ሕጉ ነው ያሉት። ይሁን እና የባህሪ ለውጥ ማምጣት ግን አንድ ቅድመ ኹኔታ ነውም ብለዋል።

ነፍሰ ጡር ሴቶች ከተወሰነባቸው ውስጥ አንድ አምስተኛውን ከታረሙ እና የባህሪ ለውጥ ካመጡ የይቅርታ ተጠቃሚ እንደሚኾኑም ገልጸዋል። አንድ የአዕምሮ በሽተኛ ኾኖ ከሚያስቸግር እና ከሚቆይ ይልቅ መለቀቁ የተሻለ እንደኾነ ከታመነበትም ያለምንም ቅድመ ሁኔታ በይቅርታ ይለቀቃል ነው ያሉት።

በቀላሉ የማይድን የጤና ችግር ያለባቸው ግለሰቦች ከተፈረደባቸው ውስጥ አንድ አራተኛውን ከታረሙ እና የባህሪ ለውጥ ካመጡ የይቅርታው ተጠቃሚ እንደሚኾኑም ዐቃቢ ሕጉ ንጉሴ ዘገየ አስረድተዋል።

ይቅርታ ከማይደረግባቸው ወንጀሎች ውስጥ ደግሞ በሀገሪቷ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 28 ላይ የተቀመጡ እንዳሉም አንስተዋል።

ለምሳሌ የዘር ማጥፍት ወንጀል የፈጸመ ሰው፣ ያለ ፍርድ የሞት ቅጣት እርምጃ የወሰደ ሰው፣ ሰውን አስገድዶ የሰወረ፣ ኢ-ሰብዓዊ የድብደባ ወንጀል ሠርቶ የተፈረደበት፣ ከ15 ዓመት በታች ያሉ ህጻናትን አስገድዶ የደፈረ እና የጠለፍ ወንጀል የፈጸመ፣ሕገ ወጥ የሰዎች ዝውውር የፈጸመ፣ ሐሰተኛ ገንዘብ መሥራት እና ማዘዋወር፣ የሽብርተኝነት ወንጀል የፈጸመ ጥፍተኛ የይቅርታ ተጠቃሚ የማይኾኑ ወንጀለኞች እንደኾኑ በመመሪያው ላይ ተቀምጧል ብለዋል።

አሚኮ








(ጥር 15/2017 ዓ.ም)የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 16ኛ መደበኛ ስብሰባው የተለያዩ ሹመቶችን ያፀደቀ ሲሆን የኔነህ ስመኝ (ዶ.ር) የኢትዮጵያ ሕዝብ ዕምባ ጠባቂ ተቋም ምክትል ዋና ዕምባ ጠባቂ አድርጎ ሾሟል።የኔነህ ስመኝ(ዶ/ር) መልካም የስራ ዘመን እንዲሆንልዎ እንመኛለን።


ስጦታ ምንድን ነው?
የታኅሳስ 21 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በስጦታ እና በውርስ መካከል ያለውን ልዩነት እና አንድነት ያውቃሉ? በኵር ጉዳዩን አስመልክቶ በአማራ ክልል ፍትሕ ቢሮ የፍትሐብሔር ጉዳዮች አቃቢ ሕግ ባለሙያ አቶ እንደግ ሰውነትን አነጋግራለች:: የዘርፉ ባለሙያ እንዳብራሩት ስጦታ ማለት በፍትሐብሔር ሕጉ በአንቀጽ 2427 በተሰጠው ትርጉም መሠረት ስጦታ ሰጭው ለስጦታ ተቀባዩ ችሮታ በማድረግ ከንብረቶቹ አንዱን ወይም ሁሉን የሚሰጥበት ወይም ግዴታ የሚገባበት ውል ነው::
ከንብረቶቹ የሚለው ቃል ስጦታ ሰጭው በሚሰጠው ንብረት ላይ ስጦታ ተቀባዩ የባለቤትነት መብት አለው:: ከዚህ በተጨማሪ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2451 ድንጋጌ ሲታይ በስጦታ የሚሰጠው ንብረት ስጦታው በተደረገበት ቀን የስጦታ ሰጭው ገንዘብ ከሆነው ንብረት ላይ ብቻ ነው በማለት መደንገጉም ይህንኑ የሚያጠናክር ነው::

የስጦታ ውሉ በሕግ ፊት የሚጸናው በፍትሐብሔር ሕግ 1678 መሠረት፦

ውል ለማዋዋል ችሎታ ባላቸው ሰዎች ሲፈፀም፣
በቂ የሆነ ፣መረጃ ያለው( እዉነተኛ የሆነ) ፣ የሚቻል እና ሕጋዊ ጉዳይ መሆኑ ፣
የውሉ አጻጻፍ (አይነት) በሕግ የታዘዘ መሆኑ ተረጋግጦ ሲፈፀም ነው::
አንቀጽ 834 እና 836 ስለስጦታ ማድረግ እና መቀበል፣ ስጦታን ማድረግም ሆነ ስጦታን ተቀብያለሁ ለማለት የሚችለው ራሱ ወይም ሕጋዊ ወኪሉ ነው:: አንቀጽ 2430 ያለዋጋ የሚሆን አገልግሎት፣ ያለዋጋ ሥራ መሥራት ወይም ያለዋጋ እቃ ለሌላ ሰው ማዋስ ስጦታ አይባልም ሲል አስቀምጦታል::
አንቀጽ 2435 የተስፋ ቃል መስጠት ወይም ስጦታ አደርጋለሁ ብሎ የተስፋ ቃል መስጠት የግድ የመስጠት ግዴታን አያስከትልም:: ነገር ግን ቃል የተሰጠው ሰው በተሰጠው ቃል ምክንያት በቅን ልቦና ጉዳይ ለመፈፀም ያወጣው ገንዘብ ካለ እንዲመለስለት ብቻ በሕግ የመጠየቅ መብት አለው::
የፍትሐብሔር ሕጉ አንቀጽ 2458 ስጦታ ተቀባይ ለስጦታ ሰጭ ቀለብ የመስጠት ግዴታ በግልጽ የተነገረ የውል ቃል ባይኖርም እንኳን ሰጭው በድህነት ላይ ወድቆ ሲገኝ ስጦታ ተቀባዩ ቀለብ የመስጠት ግዴታ እንዳለበት ያስገድዳል::

የስጦታ እና የኑዛዜ አንድነት እና ልዩነት
የስጦታ እና የኑዛዜ ውርስ አንድነት(ተመሳሳይነት) ሁለቱም አንድ ሰው የራሱን ንብረት ራሱ ወዶና ፈቅዶ ያለማንም አስገዳጅነት ለሌላ ሰው የሚያስተላልፍባቸው መንገዶች መሆናቸው ፣ ሁለቱም ተግባራት በነጻ ያለምንም የዋጋ ችሮታ የሚፈጸሙ መሆናቸው፣ ሁለቱም በፆታ ምክንያት ልዩነት የማያደርጉ መሆናቸ፣ በሁለቱም (ኑዛዜም ሆነ ስጦታ) መኖሩን የማስረዳት ግዴታ የተጠቃሚዎች መሆኑ በፍትሐብሔር ሕጉ 896 እና 2447 ተመላክቷል::
በሁለቱም ገደብ ወይም ግዴታ መጣሉን በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 916 መሰረት ተፈጻሚ ይሆናል:: ኑዛዜው አንድ ሁኔታ ሲደርስ የሚጸኑ ወይም የሚቀየሩ ሆነው ሊደረጉ የሚችል እና በ2455 ስጦታ ተቀባይ የመጦር ግዴታ ገደብ ሊደረግ ይችላል::

የስጦታ እና የውርስ ልዩነት
ስጦታ ሰጭው በሕይወት እያለ ንብረቱን ለስጦታ ተቀባዩ እንዲተላለፍ የሚፈጽመው ተግባር ነው:: ውርስ ደግሞ አውራሽ ከሞተ በኋላ ንብረቱ ከአውራሽ ወደ ሕጋዊ ወራሽ የሚተላለፍበት መንገድ መሆኑን አቶ እንደግ አስረድተዋል::
የስጦታ እና የኑዛዜ ባለመብት ለመሆን ዝምድና የግድ አስፈላጊ አደለም:: ያለ ኑዛዜ የውርስ ባለመብት ለመሆን በዝምድና መተሳሰር አስፈላጊ እንደሆነ በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 856 ተቀምጧል::
ስጦታ ማድረግም ሆነ ስጦታን ተቀብያለሁ ለማለት በውክልና እንደሚቻል በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 834 እና 836 ተቀምጧል:: የኑዛዜ ውርስን ግን በውክልና ማድረግ እንደማይቻል የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 857 ያስቀምጣል::
ስጦታ በሕግ ፊት የጸና ለመሆን በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2436 ንኡስ ቁጥር አንድ መሠረት የስጦታ ተቀባዩን ፈቃድ የሚጠይቅ ነው:: የኑዛዜ ውርስ በሕግ ፊት የጸና እንዲሆን ኑዛዜ በሚደረግበት ጊዜ ኑዛዜ ተቀባይ ፈቃዱን መስጠት አይጠበቅበትም:: ውርሱን ካልፈለገው ግን በሌላ ጌዜ ወራሽ መሆኑን አጣሪው ካሳወቀበት ቀን አንስቶ እስከ አንድ ወር ባለው ጊዜ ውርሱን አልፈልግም ማለት ይችላል ሲል በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 978 ተቀምጧል::

የይርጋ ጌዜ ገደብን በተመለከተ

ስጦታ የተደረገለት ሰው የስጦታ አፈፃጸሙን በምን ያህል ጌዜ ውስጥ መጠየቅ እንዳለበት የስጦታ ውልን በሚደነግገው የሕግ ክፍል የተቀመጠ የጊዜ ገደብ የለም:: ገደቡ ባይኖርም ግን ስጦታ ውል እንደመሆኑ ሊፈጸም የሚገባው በጠቅላላው የውል ሕግ በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1676 ንኡስ ቁጥር አንድ እና 1845 ድንጋጌዎች መሠረት ነው:: በዚህም በ10 ዓመት ጊዜ ውስጥ ስለመሆኑ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት በመታወቂያ ቁጥር 42691 አስገዳጅ የሕግ ትርጉም የሰጠ ሲሆን በወራሾች መካከል የሚነሳ የውርስ ንብረት ክርክር በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1000 ንኡስ ቁጥር አንድ በተደነገገው አግባብ በሦስት ዓመት ጊዜ ውስጥ መቅረብ አለበት::
የሟች ወራሽ የሆነ ሰው ንብረቱን በያዘው ወራሽ በአልሆነው ሰው ላይ ክስ ማቅረብ የሚችለው ደግሞ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1845 መሠረት እስከ አስር ዓመት ባለው ጊዜ ውስጥ ብቻ እንደሆነ የዘርፉ ባለሙያ አብራርተዋል::
( ማራኪ ሰውነት)
በኲር የታኅሳስ 21 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp:// www.ameco.et/Bekur
በቴሌግራም - https://t.me/bekur123 ላይ ማግኘት ይችላሉ።











20 last posts shown.